![]()
ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከመከላከያ ሠራዊቱ ጎን እንዲቆም ጥሪ ቀረበ
ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ ከመከላከያ ሠራዊቱ ጎን እንዲቆም እና ድጋፉን እንዲያደርግ የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት የሠራዊት ግንባታ ሥራዎች ዋና አስተባባሪ ሌተናል ጀነራል ባጫ ደበሌ ጥሪ አቅርበዋል።
መንግስት በወሰነው የተናጥል የተኩስ አቁም ስምምነት መሰረት ሠራዊቱ ከትግራይ ክልል መውጣቱን ያስታወሱት ሌተናል ጀነራል ባጫ በመንግስት ውሳኔ መሰረት ሠራዊቱ እንቅስቃሴ ማድረጉን ገልፀዋል።
የመከላከያ እና የአካባቢ የፀጥታ አካላት አነስተኛ ኃይል በማስቀመጥ ጥበቃ ይደረግ እንደነበር እና አሸባሪው ቡድን በተለያየ አጋጣሚ ይህንን ኃይል ለማጥቃት በመሞከር በተለያዩ አካባቢዎች ትንኮሳ ማድረጉን ሌተናል ጀነራል ባጫ ገልፀዋል።
የተናጥል የተኩስ አቁም ስምምነቱን አሸባሪው ኃይል ለመቀበል ባህሪው አይፈቅድለትም ያሉት ሌተናል ጀነራል ባጫ የተኩስ አቁም ስምምነቱን መቀበል ያልቻለው ጁንታው ከትግራይ ህዝብ የሚቀርብለትን የሰላም ጥያቄ ለመመለስ ስለማይችል እና ከህዝብ የሚነጥለው ጉዳይ ስለሆነም ጭምር ነው ብለዋል።
ህዝቡ መረዳት ያለበት “ወታደራዊ ስራ በወታደሮች እንጂ በአክቲቪስቶች የሚከናወን ስራ አይደለም፤ ጉዳዩ ውጊያ ነው” ያሉት ሌተናል ጀነራል ባጫ ሠራዊቱ በየት ቦታ፣ መቼ ማጥቃት እንዳለበት ወስኖ እየሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
የሚደረገው ጦርነት ኢትዮጵያን እንደሀገር የማስቀጠልን ጉዳይ ለማረጋገጥ እና ጁንታው የያዘውን ሀገር የመበታተን እቅድ እንደማይሳካ እና እንደማይቻል ለማሳየት ነው ብለዋል።
ሠራዊቱ እየተዋጋ ያለው ለኢትዮጵያ ድንበር ነው፤ ድንበሩ ደግሞ መረብ ነው ያሉት ሌ/ጄ ባጫ ደበሌ ሠራዊቱ የተቀመጠበትን ቦታ እና የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለማንም ግልፅ አለመደረጉንም ገልፀዋል።
ሌተናል ጀነራል ባጫ ደበሌ መከላከያ ሠራዊቱ የአገሪቱን ሉአላዊነት ለማስጠበቅ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኑንም አስታውቀዋል።

